በሚኒስትር ክቡር ዶ/ር በለጠ ሞላ የተመራ ልዑክ የአየር ላይ ቅየሳ ሥራዎች ምልከታ

በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ሚኒስትር ክቡር ዶ/ር በለጠ ሞላ እና በጂኦስፓሻል ኢንፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ቱሉ በሻ የተመራ ልዑክ የአየር ላይ ቅየሳ ሥራዎች የመስክ ምልከታ በቦሌ ኢንተርናሽናል ኤርፖርት አከናውኗል

የካቲት 29 ቀን 2014 ዓ.ም
————————————
በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ሚኒስትር ክቡር ዶ/ር በለጠ ሞላ እና በጂኦስፓሻል ኢንፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ቱሉ በሻ የተመራ ልዑክ የአየር ላይ ቅየሳ ሥራዎች የመስክ ምልከታ በቦሌ ኢንተርናሽናል ኤርፖርት አከናውኗል፡፡ በመስክ ምልከታው ስለ የአየር ቅየሳ ሥራ እና ኢንስቲትዩቱ ስለታጠቃቸው ዘመናዊ የአየር ፎቶግራፍ ካሜራ እንዲሁም ኢንስቲትዩቱ በቅርብ ጊዜ ስለታጠቀው በፍጥነት የከፍታ መረጃ ለመሰብሰብ የሚያስችለውን ዘመናዊ የላይዳር መሳሪያን በተመለከተ በአየር ቅየሳ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ከማሁ አብርሃም ገለጻ ተደርጓል፡፡
በተለይም ኢንስቲትዩቱ ወደ ሥራ ያስገባው የላይዳር ቴክኖሎጂ ዓለም ላይ ቴክኖሎጂውን ከታጠቁ ጥቂት ሀገራት ተርታ ኢትዮጵያን የሚያሰልፋት ሲሆን የከፍታ መረጃን በግብዓትነት የሚጠቀሙ እንደ መንገድ ፣ ግድብ ግንባታ ፣ መስኖና ተፋሰስ ፣ የኢነርጂ መሠረተ ልማት ዝርጋታ እና ለመሳሰሉ ቁልፍ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች የኢንስቲትዩቱ መረጃ አቅርቦት ፍጥነትና ጥራት የታከለበት እንዲሆን ከማስቻል አንጻር ጉልህ ሚና ያለው ነው፡፡
ከገለጻው በኋላ ለዕለቱ በላይዳር ቴክኖሎጂ የአየር ላይ ቅየሳ ለመስራት የበረራ ዕቅድ ለተያዘለት በኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ሊሰራ ለታሰበው ከእንጦጦ ወደ ኮተቤ የሚሄድ መንገድ የከፍታ መረጃ የማሰባሰብ ሥራ ሂደትን ክቡር ሚኒስትሩን ጨምሮ ሙሉ የልዑክ ቡድኑ ከበረራና ከአየር ቅየሳ ባለሙያዎች ጋር በበረራው ተሳትፏል፡፡ ከበረራው በኋላ ክቡር ሚኒስትሩ በዚህ ዘርፍ ኢንስቲትዩቱ ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ ቴክኖሎጂዎችን በመታጠቅ በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ በመታገዝ ለተልዕኮ ያደረገው ዝግጁነት የሚበረታታ እና ለሌሎችም አርዓያ መሆን የሚችል መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
በተጨማሪም ኢንስቲትዩቱ እነዚህን ቲክኖሎጂዎች በመጠቀም የሚያመርታቸው መረጃዎች ለሀገር ዕድገት ወሳኝ የሆኑ በተለይም መንግስት ለነደፈው የ10 ዓመት መሪ የልማት ዕቅድ መሳካት ጉልህ ሚና ስላለው ከተለያዩ ሴክተር ተቋማት ጋር ቅንጅታዊ አሰራር በመፍጠር የበለጠ ሀገራዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ በሚደረገው ጥረት ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል፡
 

Comments are closed, but trackbacks and pingbacks are open.

This website uses cookies to improve your experience. We'll assume you're ok with this, but you can opt-out if you wish. Accept Read More